8 ኮሎኔሎች እና አንድ ከፍተኛ የሕወሓት ጀነራል ቦራ አካባቢ ተደመሰሱ | ጄነራል ጻድቃን መሆኑ አልተረጋገጠም | ጀነራሉ በክብር የተቀበረ ይመስላል ተብሏል

(ዘ-ሐበሻ ዜና) የተቆራረጠው የሕወሓት ኃይል ያለ የለለ ኃይሉን በማጠራቀም ከተከበበት ለመውጣት በሚያደርገው መፍጨርጨር ከፍተኛ ውድመት እየደረሰበት መሆኑን ዘ-ሐበሻ ከመከላከያ ምንጮች ማምሻውን ያረጋገጠው መረጃ አመለከተ። እንደመረጃው በአማራ እና ትግራይ ድንበር አካባቢ በማይጨው አቅራቢያ ቦራ፣ ጮቅሏ፣ ጨሌና፣ አላጄ፣ አሚላ፣ አምባላጌ፣ በተባሉት ከተሞች ትርፍራፊው የሕወሓት ኃይል ውጊያ ከፍቶ በመከላከያው እና በአማራ ልዩ ኃይል ተደምሷል። ቅድሜና እሁድ በአምባላጌ አካባቢ በተደረገ ውጊያ ከ180 በላይ የሕወሓት ወታደሮች የተደመሰሱ ሲሆን በሎጅስቲክ እጥረት 360 ዲግሪ የተከበቡት የሕወሓት ትራፊ ኃይሎች ኃይላቸውን በማሰባሰብ ከትናንት ጀምሮ በቦራ አካባቢ ሰብረው ለመውጣት ውጊያ ከፍተዋል።

በውጊያውም ሕወሓቶች ትናንት ቦራን በድጋሚ መቆጣጠራቸውን ሲገልጹ የነበረ ሲሆን በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ መካለከያ ሰራዊት በወሰደው እርምጃ ከ200 በላይ የሕወሓት ሰራዊት አባላትን ደምስሷል።
የተደመሰሱ የሕወሓት ኃይሎች ፎቶግራፎችም ጭምር ዘ-ሐበሻ እጅ የገቡ ሲሆን ከሞራል አኳያ ምስሎቹን ከማሳየት ተቆጥበናል።

እንደ መከላከያው ምንጭ ከሆነ ቦራ ላይ በተደረገ ውጊያ ማንነታቸው የሚታወቅ 8 ኮሎኔሎች እና ሌሎች ማንነታቸው ያልታወቀ ከፍተኛ የሕወሓት የጦር መኮንኖችም ተደምስሰዋል። ማንነቱን ለመለየት ያስቸገረ ጀነራልም ተቀብሮ እንደተገኘ አክለዋል። ምንጩ እንደሚሉት የኢትዮጵያ መካለከያ ሰራዊት ቦራን በ እጁ ሲያስገባ አንድ ጀነራል በክብር እንደተቀበረ በሚያሳይ መልኩ አስከሬኑን እንዳገኙ ገልጸው ማንነቱን ለመለየት እንደተቸገሩ ገልጸዋል። በዚህ አካባቢ ጦሩን ይመሩ የነበሩት የቀድሞው የኢትዮጵያ ኢታማዦር ሹም ጄነራል ጻድቃን ገብረትንሳኤ እና በፌዴራል ፖሊስ የ እስር ማዘዣ የወጣባቸው ብርጋዴር ጀነራል አብርሃ ተስፋዬ በርሄ (ድንኩል)ነበሩ። አንዳንዶች ጄነራል ጻድቃን እንደተገደሉ ቢናገሩም የዘ-ሐበሻ ምንጭ ግን ጄነራሉ ራሰ በረሃ እና ወፍራም እንደሆኑ ገልጸው አስከሬን ለቀናት ሲቆይ ራሱን ስለሚቀይር ለመለየት እንደተቸገሩ ለጊዜው ማንነቱ ያልታወቀ በሚል ቢገለጽ የተሻለ ይሆናል ሲሉ ነግረውናል።

በአካባቢው ከፍተኛ ውጊያ እየተደረገ መሆኑን የሚገልጹት ምንጩ፤ በውጊያው የተማረኩ የኢትዮጵያ ወታደሮች በሚል የሕወሓት ሚዲያዎች እያሰራጯቸው ስላሏቸው ምስሎች ጠይቀናቸዋል። ምንጩ እንደሚሉት “ሕወሓት አሁንም ድረስ ሰሜን እዝን ከመታ በኋላ ካፈናቸው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት አሁንም የተወሰኑትን በየሄደበት ይዟቸው እየተዟዟረ ነው። የቀደሞ የሰሜን እዝ አባላትን ነው አሁንም እንደ አዲስ ማረኩኝ እያለ የሚያሳየው” ብለዋል።

እንደምንጩ ገለጻ የተራረፈው የሕወሓት ኃይል እንኳን ለማመማረክ ቀርቶ ከገባበት ቀለበት ለማምለጥ የተቸገረበት ሁኔታ ነው ያለው፤ ሆኖም ግን እንደመያዣ አሁንም ድረስ ይዟቸው የሚዞራቸውን የተወሰኑ የሰሜን ዕዝ አባላት ለፕሮፓጋንዳና ከደጋፊዎቹ ገንዘብ፤ ለውጭ ሃገራት ደግሞ አሁንም አቅም እንዳለው ለማሳየትና እንዲያደራድሩት ማረኩኝ በማለት ምስላቸውን እያነሳ እየተጠቀመበት ይመስላል ይላሉ።

ካለፈው አርብ ምሽት ጀምሮ የተከበበው የሕወሓት ኃይል ሰብሮ ለማምለጥ ያልፈነቀለው ቦታ የለም። ለዚህም የመረጠው በአምባላጌ በኩል ሰብሮ መውጣት ነው። በዚያ አካባቢ የአማራ ልዩ ኃይል ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ሞክሮ አልተሳካም። እቅዳቸው እየገፉ ሄደው በአፋር አርገው ወደ ጅቡቲ መሪዎቻቸውን ለማስመለጥ ይመስላል የሚሉት ምንጩ በርካታ የሰራዊታቸው አባላት ተማርከዋል ይላሉ።
ቦራ አካባቢ በተደረገው ውጊያ ከጦሩ አዛዥ ጄነራል ታደሰ ወረደ ውጪ ሁሉም የተሳተፉ ይመስላል የሚሉት ምንጩ ለዚህም 8ማንነታቸው የታወቀ ኮሎኔሎቻቸው እንዲሁም ማንነታቸው ያልተለየ ሌሎች አዛዦች ተደምሰሰዋል ይላሉ። ጄነራል ታደሰ ወረደ የሚመሩት የተራረፈው ኃይል ከጌታቸው አሰፋ ጋር በመሆን በዋግህምራ አቅራቢያ አርበጌሌ አካባቢ ታይተው መከላከያው ሲመጣባቸው መሰወራቸውን የሚገልጹት ምንጮች እነርሱንም የማሳደዱ ተልዕኮ እየተሰራበት ነው ብለዋል።

ከመንግስት በኩል ሕወሓት በሰሜን ዕዝ ላይ እርምጃ ከወሰደ በኋላ እስካሁን የጠፉትን እና የደረሱበት ያልታወቀውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት ማንነት አለመግለጹ አሁን ህወሓት እንደማረከ በማስመስል ይዟቸው ከከተማ ወደ ከተማ የሚዘዋወረውን የሰራዊቱን አባላት ለፕሮፓጋንዳ እንዲጠቀምበት በር ከፍቷል ብዬ አስባለው የሚሉት ምንጩ መንግስት ይህን በቶሎ እንደሚያርም እና በሰሜን ዕዝ በሕወሓት ሰራዊት ታግተው እስካሁን ደብዛቸው ያልተገኘውን የሰራዊት አባላት ይፋ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
በአሁኑ ሰዓትም የተራረፈውን የሕወሓት ኃይል የመደምሰሱ ተልዕኮ እንደቀጠለ ነው ያሉት ምንጩ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ለኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቀርበዋል።
በጉዳዩ ላይ መረጃ ለማግኘት ወደ የመከላከያ ኢንዶክትሪኔሽን ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሜጀር ጀነራል መሐመድ ተሰማ ደውለን እንደተለመደው ስልካችንን አላነሱም። በአዲስ አበባ የሚገኘው መከላከያ አመራር በዛሬው ዕለት ስብሰባ ላይ እንደነበር ከምንጮች ሰምተናል። ሆኖም ግን ስለመከላከያው ወቅታዊ ሁኔታ መረጃ ለመስጠት ኃላፊነት የተሰጣቸው ሜጀር ጀነራል መሐመድ ተሰማ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እየተወጡ አለመሆኑ በተደጋጋሚ ከጋዜጠኞች ወቀሳ እየተሰነዘረባቸው ይገኛል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ድረገጽ ከ4 ወር በላይ ከአገልግሎት ውጭ መሆኑን ዘ-ሐበሻ ከአንድ ወር በፊት ለሕዝብ መረጃውን ይፋ አድርጎ ሜጀር ጀነራል መሐመድ ተሰማ ይህን ቶሎ እንዲያስተካክሉ በይፋ ጥቆማ ቢሰጥም ድረገጹ ዛሬም ድረስ አገልግሎት እየሰጠ አለመሆኑ፤ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት መረጃ ቶሎ ለሕዝብ በማድረስ ረገድ ድክመት እንዳለበት አንዱ ማሳያ ነው የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች አሉ።
ይህ በ እንዲህ እንዳለ የራያ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ አመራር ደጀኔ አሰፋ እየተካሄደ ባለው ውጊያ ዙሪያ ደረሰኝ ያለውን መረጃ አጋርቷል። የደጀኔን መረጃ ደግሞ እንደወረደ እንደሚከተለው አቀርብላችኋለሁ።

የተራረፉት የጁንታው ሃይሎች በጀግናው መከላከያ ሰራዊታችን እየፀዱ ይገኛል!!!! ከቆላ ተንቤን እና ከተከዜ በርሃ እንዲሁም በልዩ ልዩ ቦታዎች ውስጥ ተደብቀው የነበሩት የጁንታው ርዝራዦች በመከላከያ እየተሳደዱ ጥሻ ለጥሻ በመሸሽ ወደ ራያ አካባቢ ማይጨው ቦራ የመጡ ሲሆን ከዚያም ሲከበቡ ወደ ራያ ኦፍላ ኮረም ልዩ ቦታው ፀልጎ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በአንድ ላይ ተጠራቅሞ የነበረውን የጁንታውን ትርፍራፊ ኃይል መከላከያ ሰራዊት በአራት አቅጣጫ በመክበብ ለሶስት ቀናት ያህል ያለ እረፍት በማጥቃት በመቶዎች የሚቆጠሩትን የደመሰሰ ሲሆን በርካቶቹን ማርኳል!!!! ይህንን የሚገልፁ ብዙ ፎቶዎች የደረሱኝ ቢሆንም ከዚህኛው በቀር ሌሎቹን ማጋራት አልፈለግኩም:: ይህ የምትመለከቱት ፎቶግራፍ ከመከላከያ ሰራዊት ከድቶ ጁንታውን የተቀላቀለ ከፍተኛ የጦር መኮንን የነበረ መሆኑ ታውቋል!!! በተደረገው የማፅዳት ዘመቻ ተሰናብቷል!!! የአይን እማኞች እንደነገሩኝ ከወደቁት ሁሉም አስከሬኖች ላይ ሃሺሽ (ዕፀ ፋሪስ) እና በሃይላንድ ፕላስቲኮች የተሞሉ የአልኮል መጠጦች ተገኝቷል!!! ሃሽሽ እያስጨሰ እና በባዶ ሆዳቸው አልኮል እያጠጣ በማስከር አብዛኞቹን ጁንታው አስጨርሷቸዋል!!! ይህንኑ ሃቅ በመከላከያ የተማረኩ ራሳቸው የጁንታው ምርኮኞችም አረጋግጠዋል ብለውኛል!!! በርግጥ ጁንታው ቀድሞም ቢሆን በሃሽሽ እና በአልኮል ወጣቶችን እያደነዘዘ በጦርነት ይማግድ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን ዛሬም ከነ ክፋቱ ወደ መቃብር እየወረደ ነው!!! ከምግብ እጦት ብዛትም ሰውነታቸው እጅግ መጎሳቆሉም ታውቋል!!!! ህዝቡም ምግብ በማዋጣት ስለሰለቼ የጁንታውን ትርፍራፊ ኃይል ከአካባቢው እንዳራቃቸው ለማወቅ ተችሏል!!!! ይህ በእንዲህ እንዳለ አንድ የጁንታው ከፍተኛ የፖለቲካ አመራር በአካባቢው እንደነበረ የተነገረ ሲሆን መሮጥ አቅቶት በአህያ ላይ ተጭኖ ለጥቂት እንዳመለጠ ምርኮኞቹ እና ያዩት ሰዎች መናገራቸውን መረጃዎቼ አድርሰውኛል!!!! በአህያ አምልጦ የትም አይደርስም ብለውኛል!!!! አሁን አካባቢው ሙሉ በሙሉ ስለተከበበ በአጠቃላይ አሁን የቀሩትን fugitives ሽፍቶች በአጭር ቀናት ፍፃሜያቸው እንደሚታወቅ መገመት ይቻላል!!! ይህንን የፅዳት ዘመቻ በአፋጣኝ በማጠናቀቅ ነጮቹ በዚህ ባለቀ ሰዓት ከጁንታው ጋር ተደራደሩ የሚሉትን ፈሊጥ አፈር ከድሜ ማስበላት ግድ ይላል!!!! በስንት መስዋዕትነት የተገኘውን ድል እስከመጨረሻው ማስጠበቅ የመንግስት እና የመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሃላፊነት ነው!!!! ድርድር የሚባል ነገር አይታሰብም!!! ዶክተር ቴድሮስ እነዚህን ሁለት ቀናት እንደ እብድ ያደረገው ነገርየው እየተጠናቀቀ መሆኑን ስለሚያውቅ በብስጭት እና በተስፋ መቁረጥ መሆን አለበት!!!!ነጮቹም ይሄው መረጃ ስለሚደርሳቸው ከጁንታው ውስጥ ሁለት ወይም ሶስት ባለስልጣናትን ለማስተረፍ በመጭዎቹ ቀናት ሊረባረቡብን ስለሚችሉ መዘጋጀት ተገቢ ነው!!! ተደራደሩ ሊሉ እንደሚችሉ ማሰብ አይከብድም!!!! በደብረፅዬን ስም ተፃረ የተባለው እና ዛሬ የተጋለጠው የደብዳቤ ሴራ የዚሁ አካል እንደሚሆን መገመት ይቻላል!!!!! የነጮቹ ጫና በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ከግራ እና ከቀኝ ቢበዛም እኛ ግን ፅዳቱን በቶሎ በማጠናቀቅ ወደ ሌላ ሃገራዊ ጉዳያችን መሻገር አለብን!!!! ክብር ለጀግናው መከላከያ ሰራዊታችን!!!!